አሁን አይኔ አየ ….የቴዲ አፍሮ የፍቅር ክታብ !
(አሌክስ አብርሃም)
ቴዲ አፍሮ ግጥምና ዜማ አቀናጅቶ የሚዘፍን ድምፃዊ ብቻ አይደለም …ቴዲ የነበረውን ታሪክ እየመዘዘ በጎውን ይበል .. መጥፎውንም እንዳይደገም እያለ ከታሪክ ማህደር እኛነታችንን የሚተርክ ንቡር ጠቃሽ ነው ብያችሁ ነበር…ግን ይሄንንም ብቻ አይደለም …ልጁ ከውብ ሴት እግር ስር ተንበርክኮ ‹‹አንች ጋር አድሬ ሲነጋ ልሙት›› አይነት አልፎ ሂያጅ ፍቅር ሰባኪ አይደለም …ቴዲ ለእኔ ፈላስፋም ጭምር ነው …ቀላል ይፈላሰፋል! ያውም ነብስያችን ላይ ነዋ!! በቀደመው ፅሁፌ ‹‹የቴዲ ገፀ ባህሪያት ተራ ሰዎች አይደሉም ለአገራቸው የሚጠበቅባቸውን በሚገባ የተወጡ ምጡቅ ሃላፊነት የሚሰማቸው ነፍሳት ናቸው ›› ብያችሁ ነበር … አሁን አንዷን ገፀ ባህሪ መዝዠ ለዚህ አባባሌ እማኝ ላቀርባት ነው …. በሉ ሙዚቃዋን ከፍ አድርጓትና ጨዋታችንን እንዲህ እንቀጥለው . . .
በመጀመሪያ ምደርም ባዶ ነበረ ጨለማም በባዶው ላይ እንዲል ቅዱስ መፅሃፉ የሰው ልጅ ሲፈጠር ባዶ ነው …ሲጀመር የወላጅ ድጋፍ ሲቆይም የቤተሰቡ …የጎረቤቱ …የመንደሩ ….የአገሩ ፍቅር እንደእህል ውሃ በውስጡ ህያውነትን እየገነባ ያሳድገዋል …የሰውን ልጅ ሰፊ ባዶነት መሙላት የሚችል ብቸኛ ተአምር ፍቅር ብቻ ነው ! ሰዎች እየተናቆሩ እየተናከሱ እንኳን አብረው የሚኖሩበትን ከተማ ይመሰርታሉ ለሰው መድሃኒቱ ሰው የመሆኑ ሚስጥር የነፍስያ ሃቅ እንጅ ባዶ ፍልስፍና ወይም አባባል አይደለምና !!
ዛሬ ለእኔ የምንግዜም ምርጥ ፍልስፍና የሆነውን የቴዲ አፍሮ አንድ ዘፈን እንደሰማሁት ላሰማችሁ ይሄው ነገሬን ከስሩ ጀመርኩት ! ከዘፍጥረት!! ለምን ከዘፍጥረት ….ነገሩ ወዲህ ነው !
ጥንት እዚህ ባቡር ጣቢያው ከፍ ብሎ ካሉት ጭርንቁስ መንደሮች በአንዱ አንድ ድንቡሽ ያለ አይነ ስውር ህፃን ልጅ … ነጭ ብትሩን ይዞ ከጨርቅ የተሰራች የደብተር መያዣ ኮሮጆውን አንግቶ …ባቡር መምጣትና አለመምጣቱን በንቁ ጆሮዎቹ አጣርቶ ሃዲዷን ተሸግሮ ወደትምህርት ቤት ይሄድ ነበር …ታዲያ እሱ አለሙን ሁሉ ነጭ ይሁን ጥቁር ባይመለከትም ምንጊዜም ከኋላው የእናቱ አይኖች እንደመልአክ ክንፍ ተዘርግተው ይከተሉት ነበር …. ከእናት ፍቅር ከሚመነጭ ጾለት ጋር! ህፃኑ እየራቀ... እየራቀ ከእናቱ እይታ ሲሰዎር ግን ሰፊው አለም ውስጥ ማንም የለውም …ብቸኛ ህፃን ነው … የህፃናት ጨዋታ ይሰማዋል ….ኳስ እየጠለዙ …እተሯሯጡ ….አይነስውር ነውና የህፃን ልቡ እንደልጆቹ መቦረቅ ባለመቻሉ ክፉኛ እያዘነች ጥጉን ይዞና ምርኩዙን አቅፎ አለሙን በጆሮው ልክ እየሰፈረ በብቸኝበት ይኖር ነበር ….
ይህን ህፃን በስሙ እንኳን የሚያውቀው ሰው አልነበረም ….በቃ ማንም ሰው ስለዚህ ሚስኪን ልጅ የሚያወራ ጉዳይ ካለው ‹‹ባለምርኩዙ ልጅ ›› እያለ ያወራል አገር የሚውቀው ከሰውነቱ በላይ …በነጭ ምርኩዙ ነበር …አንዳንዴ ጉድለታችን አይደል መታወቂያችን ….ከጉድለታችን አሸግረው ሙላታችንን የሚታዘቡ ጥቂቶች በጣም ጥቂቶች ናቸው ! እንዲህ ይለዋል ቴዲ በውብ ዜማና ግጥሙ የነበረውን ሲተርከው …..
አይኖቸ አያዩ ብርሃን የላቸው
በልጅነቴ ድሮ አጥቻቸው . . . .
ልቤን ተሰማው እንግዳ ነገር
ምርኩዝ ይዠ ነው የሚያውቀኝ አገር
አይኖቸ አያዩ ብርሃን የላቸው
በልጅነቴ ድሮ አጥቻቸው . . . .
ልቤን ተሰማው እንግዳ ነገር
ምርኩዝ ይዠ ነው የሚያውቀኝ አገር
እናም በእነዚህ የብቸኝነት ምልልሶች …በእነዚህ ከባድ የጨለማ ዘመኖች በእነዚህ የመገፋት ዘመኖች ….በአንዱ ቀን ይህችው ብቻዋን ጭል ጭል የምትል የህይዎት ብርሃን እናቱ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በሞት ተለየችው …..አሁን ጨለማው ሙሉ ሆነ ድቅድቅ ጨለማ !! ማሙሽ በአካልም በስነልቦናም በጨለማው ውስጥ አደገ ! በዚህ ጉዞው ውስጥ ብቸኛ በዚች አለም ያለችው ዘመዱ የቅርብ ወዳጁ ምርኩዙ ብቻ ነበረች !! ከፊቱ ቀድማ እሱም ዳናዋን የሚከተላት አጋሩ !!
የብቸኝነት ጎምዛዛ ጣእም አፉ ላይ ይሰማው ጀመር … የችግሩ ግዝፈት ከማህበረሰቡ አመለካከት ጋር ተዳምሮ የአእምሮውን ጓዳ በጭንቀትና በመራር እውነት ሞላው ….በእርግጥም ሁሉም ነገር ጨለማ ነበር …ይህን ግዙፍ ጨለማ ከምን ጋር እናወዳድረው …ገና ከዘፍጥረት ምድር ስትፈጠር ለብሳው ከነበረው ጨለማ ጋር ….በትክክል!! ….እናም ድምፃዊው በአደባባይ ‹‹ፍቅር እግዚአብሔር ነው ›› አላለም …?? ይሄው ልክ ሲመጣ ….እግዚሃር ደግሞ ብርሃን ነው ይላል መፅሃፉ …እናም በዘፍጥረት …. የፍቅር አምላክ ከላይ ከሰማይ የፈጠራትን ምድር ሲቃኝ እማይበጃችሁ ይጨልምበት ጥቅጥቅ ያለች ጨለማ …!! እግዚአብሔር ፍጥረት ጨለማ ውስጥ ሲቀመጥ አይወድም …ሁላችንም በብርሃን እንመላለስ ዘንድ ፈቃዱ ነውና እንዲህ አለ ‹‹ብርሃን ይሁን ›› ቃሉን ተከትሎ አለም በብርሃን ተጥለቀለቀች ይሄው እስከዛሬ ቀን በፀሃይ ማታም በጨረቃ ብርሃን ከምድር ተለይቶ አያውቅም ! እግዚአብሔር ብርሃን ይሁን ካለ ዘላለማዊ ብርሃን ነውና !!
ወደቴዲ ገፀ ባህሪ እንመለስና የነገራችንን ውል ከዘፍጥረት ምሳሊያችን እናገናኘው ….ያች የህፃኑ ሚስኪን እናት ልትሞት ስታጣጥር ለልጇ በምድር ላይ ካሉት ነገሮች ሁሉ ከፍ ለውን ነገር ያገኝ ዘንድ መርቃው የመጨረሻ እስትንፋሷን ሳበች በቃ! ደሃ እናት ለልጇ ልታወርሰው ምትችለው የመጨረሻ ነገር የልብ ፍቅርና ምርቃቷል አይደል ..እሱን አወረሰችው ….ዘፋቡ እንዲህ ይለናል ስረፍቅር ውርሱ ወዲህም ስለእናቱ ምርቃት ነጆሮው የሰማውን ቃል ስምረት ሲያስረዳን …
መሽቶ አይኔ በልጅነቴ
መርቃኝ ስትሞት እናቴ
በፍቅር ብራ እንዳለችኝ
መርቃኝ ስትሞት እናቴ
በፍቅር ብራ እንዳለችኝ
አንች ላይ ወስዳ ጣለችኝ !!
ይሄዋ እናቱ የመጨረሻ ምርቃት ‹‹በፍቅር ብራ ›› የሚል ነበር …ይች ብልህ እናት በጨለማ ውስጥ ተፈጥረው በጨለማ ውስጥ ቢያድጉም እንኳን በፍቅር መብራት እንደሚቻል ጠንቅቃ ያወቀች ነበረች …እናም ምርቃቷን በመነመነ የመጨረሻ ትንፋሽ ወደልጇ ተኮሰችው ‹‹በፍቅር ብራ›› እግዜሩ ከሰማየ ሰማይ ይችን ምርቃት ሰማ እናም እንዲህ አለው ለዚህ በጨለማ ለኖረ ልጅ ‹‹ብርሃን በህይወትህ ላይ ይሁን ›› ….ቦግ አለ ወዲው !! እግዜር ነዋ ተናጋሪው ! ህፃኑ ወዲያው አለምን ወለል አድርጎ ተመለከታት ከነስንክሳሯ ከነውበቷ ….ከነመልካም ነገሮቿ ….እንዴት አለምን አየ …አይነስውር ነው አላልክም …ብለሁ!! እና የስጋ አይኑ በራለት …አልበራም!! እና ….እናማ አየ በቃ ማየት ቻለ …ፀሃይ አልነበረም ብርሃኑ ጨረቃም አልነበር …ልክ እንደእናቱ ምርቃት የፍቅር ብርሃን ከነፍሱ ጥግ ቦግ ብሎ በራ !! እናም ዘፋኙ ምርኩዙን አስቀምጦ በደስታ እንዲህ አለ ….
የምየ ሰምሮ ትንቢቷ
ወዳጅ አገኘሁ ካንጀቷ
ኩራዜን እንዲህ እንደማይ
አንች ነሽ ላምባዲናየ
አሁን አይኔ አየ!!!!!
ወዳጅ አገኘሁ ካንጀቷ
ኩራዜን እንዲህ እንደማይ
አንች ነሽ ላምባዲናየ
አሁን አይኔ አየ!!!!!
ይሄው ነው የብርሃኑ ምንጭ የምትወደው ከምርኩዙ አልፋ በእሱነቱ የምታውቀው የነፍስ ፍቅረኛ አሻረው (ሰጠው ያንሳል ቃሉ) እናም ይሄ ወጣት በራለት …በርቶለት ብቻ አልቀረም የዘመናት ብቸኝነቱ ውስጥ ውስጡ የተጠራቀመው እውነት በፍቅር ክብሪት ተለኮሰና እንደርችት በውብ ብርሃኑ ወደውጭ በዙሪው ወዳሉ ሁሉ ይረጭ ጀመረ …ፍቅርን ሰበከው …እኛም ሰማን እንዲህ ይላል ድምፃዊው …ላምባዲና በሆነችለት ውብ ነፍስ ላይ ተደላድሎ አይናማ ነን ብለው ለሚኮፈስቱ ሁሉ …ፍቅርን ወደልብ ካላንቆረቆረ በስተቀር ይሄን ለምልክት የተቀመጠ አይንህን እንዳትኮራበት …ፍቅር የሌለው አይናማ ዛሬም በጨለማ ውስጥ እየተደናበረ ነው ….የአለም ብርሃን አንድ እሱም ፍቅር ብቻ ነው !! ከውድ አምፖሎች በሚመነጭ የኤሌክትሪክ ብርሃን የተሸቆተቆጠ ሳሎን ውስጥ ብትኖርም ቅሉ ፍቅር ልብህ ውጥ ከሌለ ተበላህ ጓድ …ቦግ ያለ ጨለማ ውስጥ ነህ …ቦግ ያለ ጨለማ !! ስንቱ መሰለህ አይኑ አፍጥጦ ፍቅር በእግሩ ስር ሲልፍ የማይታየው …ይሄ ነው መታወር ! ይለናል ድምፃዊው …እንዲህ በዜማ
እንዳትኮራበት አይንህን
ፍቅር ያልነካው ልብህን
ፍቅር ያልነካው ልብህን
ይገርማል ብለን ልንሄድ ስንነሳ … ቆይ አልጨረስኩም …. ምን ቀረ ስንል
በማየት ስለማትበልጠኝ
ና መነፅሬን ለውጠኝ ! ኧረ ምርኩዙንም ይውሰድ እኛ ደግሞ !ሃሃ ነዋ ...ስንቱ ነው ፍቅር አልታው ብሎ ወይም ፍቅር የሚመስል ሞቅታ ተከትሎ ገደል የገባ …እህ ብትል ግማሹ ህዝብ ከገባበት ገደል እስካሁንም አልወጣም አንዱ በአንዱ ላይ እዛው እየተነባበረ …እና የፍቅር ምርኩዝ ከማቀበል የበለጠ በጎነት ከየት ይመጣል! ያዝ ይሄን ምርኩዝ ጀመዓው !! እንዲያ ነው ፍልስፍናው ለኔ!!
በማየት ስለማትበልጠኝ
ና መነፅሬን ለውጠኝ ! ኧረ ምርኩዙንም ይውሰድ እኛ ደግሞ !ሃሃ ነዋ ...ስንቱ ነው ፍቅር አልታው ብሎ ወይም ፍቅር የሚመስል ሞቅታ ተከትሎ ገደል የገባ …እህ ብትል ግማሹ ህዝብ ከገባበት ገደል እስካሁንም አልወጣም አንዱ በአንዱ ላይ እዛው እየተነባበረ …እና የፍቅር ምርኩዝ ከማቀበል የበለጠ በጎነት ከየት ይመጣል! ያዝ ይሄን ምርኩዝ ጀመዓው !! እንዲያ ነው ፍልስፍናው ለኔ!!
ፍቅር የሌለው አይናማ
ውጦታልና ጨለማ !!
ሰው ወዶ ሰው ያልወደደው
ውጦታልና ጨለማ !!
ሰው ወዶ ሰው ያልወደደው
መርኩዜን መጥቶ ይውሰደው !! ይልሃል ቴዲ !ሃቅ ነው እንላለን እኛም !!በተወደድነው ልክ እንደውም በቻልነው መጠን ብንወድ ምን ይጎድልበናል አቃቂር እያወጣን ጉድለት እያፈላለግን ከመጥላት የነብስያ መቀጨጭ እና በጫጨት እንጅ ድሎት አይገኝ !! ውሰዱ ብለናል የፍቅር ምርኩዝ (እንደውም ማስታወቂያ ….አዲሱን አመት ምክንያት በማድረግ ለመላው የሰው ልጅ የፍቅር ምርኩዝ በዚህ ይገኛል ….በቅናሽ ሳይሆን በነፃ …ተጦሃርቶ መምጣት ነው ዋጋው ) ማነህ ይሄን ማስታወቂያ ከዳር እስከዳር በዘጠና ሚሊየን ኮፒ አባዝተህ ለጥፍልኝ !!
ያይኔ መቅረዙ ባዶ ነው
ማየት ለብቻው ምንድነው
ሳያይ ያመነ ሲጠራው
እይ ፍቅር መጥቶ ሲያበራው !! አሜን እንል ዘንዳ እዚህ ጋ እንገደዳለን !!
ማየት ለብቻው ምንድነው
ሳያይ ያመነ ሲጠራው
እይ ፍቅር መጥቶ ሲያበራው !! አሜን እንል ዘንዳ እዚህ ጋ እንገደዳለን !!
አሁን አየ አይኔ …….እንግዲህ እኔም የቴዲን ላምባዲና እንደበራልኝ ወደእናተ አመጣሁት … እንዲህ ሲዘፈን እንዲህ ብንሰማ አይፈረድብንማ …ኪነጥበብ የነፍስ ሃቅ ነው አላልንም ….ኪነጥበብ ቤት መምታት ሳይሆን በእያንዳንዱ ሰው ቤት ውስጥ መግባት ነው አላልንም …ለዛ ነው ለተዲ በራችንን ከፍተን ያስገባነው እንላለን ወደፊት ለሚመጡም የመወደዱ ሚስጢርም አልገባንም ላሉ ሁሉ !! በነገራችን ላይ ላምባዲና ታውቃላችሁ … ለማታውቁ በጣም በድሮ ጊዜ ውስጡ ላምባ የሚሞላበት እንደኩራዝ አይነት ቤት ውስጥ ለመብራትነት የሚጠቀሙበት ቆርቆሮ ነበር …የእጅ ባትር በሚኒሊክ ዘመን ሲመጣ ስያሜው ለእጅ ባትሪ ተላለፈ ….በገጠር ወንድ ልጅ የእጅ ባትሪውን ከእጁ አይለይም መሪው ናት …ለአደጋ ጊዜ ተግ የሚያደርጋት ጨለማውን መግፈፊያው ናት …ቴዲ ላምባዲና ሲላት ፍቅሩን እውነት አለው !!
አለም ታየችኝ ባንች ውስጥ ሁና
በፍቅር ኩራዝ በላምባዲና !!
በፍቅር ኩራዝ በላምባዲና !!