------///----- ቀጠሮ -----/// ------
/በጋዜጠኛ ሙሉጌታ አንበርብር፣ /
.
ከዋክብት ቢያብቡ ብትደምቅ ጨረቃዋ
ሲነጋ ይጠፋል ያ ሁሉ ማዓዛዋ
ከእንቅልፍ ለመንቃት ስዓቱ ተቀጥሮ
ነግ ለመገናኘት ዛሬ ተነጋግሮ
ውልደት; ሞት ጋብቻ እና ኑሮ
ክፋት ና ደስታ ሁሉም በቀጠሮ
ልጅም ይወለዳል ዘጠኝ ወር ተቆጥሮ
.
ይህም በቀጠሮ
ህፃናት ቢቦርቁ ዛሬን ቢደሰቱ
መጭውን አያውቁም እንዲህ ሲጫዎቱ
.
ይህም በቀጠሮ
ወጣት ቢያሸበርቅ ቢዋብ በቁሳቁስ
ያጌጡበት ገላ አይቀር መፈራረስ
.
ይህም በቀጠሮ
ወጣቱም በፍቅር ልቡን አደንዝዞ
ያወጣል ያወርዳል በለሆሳስ ፈዞ
እሷም በተራዋ በፍቅሩ ተይዛ
ፍቅሯንም ትገልፃለች እንዳጢያት ተናዛ
.
ይህም በቀጠሮ
ስዓታት ቀናቶች ወራትን ወላልደው
መች ቀሩ ቀናቶች እንዲህ ተፍራርቀው
ወራትም ነጎደ አመትን ተክቶ
መሸምገል አይቀርም እንዲሁ ጃጅቶ
ሲንቀሳቀስ ሲውል ከምርኩዙ ጋራ
ሲላተም ይውላል ከትዝታው ጋራ
.
ይህም በቀጠሮ
አሰሪው ለማዘዝ ሰሪው ለመታዘዝ
ስዓቱን ለማድረስ ይውላል ሲናውዝ
.
ይህም በቀጠሮ
ዛሬን ተሰይሞ በሃሳብ ነውሎ
ለነገ ቀጥሮል በምናቡ ስሎ
እግዜርም ቀጥሮል የምፃዓት ቀን ብሎ
ይህም በቀጠሮ
ታዲያ ወዴት ልሂድ ወደየትስ ልግባ
ቀጠሮ ሲሰማ መንፍሴ አንዳይባባ
No comments:
Post a Comment